ኢትዮጵያዊው ጆርጅ ኦርዌል

Standard
ፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማሪያም- የወደብ መብራት ሦስት
     መቼም ‘Animal farm’ን የሚተካከል ተሳልቆ (ሳታየር) አላነበብንም፡፡የዚህ መጽሐፍ ደራሲ የብዕር ስሙ ጆርጅ ኦርዌል ሲሆን ትክክለኛ ስሙ ኤሪክ ብሌር ይሰኛል፡፡ዛሬ ስሙን ላነሳሳው የፈለኩት ያን ጋዜጠኛ፣ መምህር ፣ ወታደር እና የተባ ብዕረኛ ሳይሆን ኢትየጵያዊውን ጆርጅ ኦርዌል ነው ፡፡

      ይህ ኢትዮጵያዊ መምህር ፣የካርታ እና ጂኦግራፊ ባለሙያ ፣ የዕድሜ ልክ ሐያሲ ፣ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ፣ በምክንያት ፓለቲከኛ ሲሆን የኛን እንስሳት ዓለም ለማሳየት እንደጆርጅ ኦርዌል ልብወለድ መጻፍ አላስፈለገውም፡፡ ለብዙ አመታት  ስለ ሕገ አራዊትና ሕገ ሐልዮት  በግልጽ እየተነተነ አሳየን  እንጂ፡፡ ሰው እንድንሆን  መሞገት ከጀመረ እንደሰነበተ የምንረዳው ከሁለት አገዛዞች በፊት  በአዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት በተደረገ የዕድሮች ስብሰባ ያደረገውን ንግግር  ስናነብ ነው፡፡ Continue reading

ሐዋሪያቲሁ ክበበ ፣ እግረ አርዳኢሁ ሐፀበ፤ ኮኖሙ አበ ወእመ ፣ ወመሐሮሙ ጥበበ፡፡

Standard

       ሰሙነ ሕማማት “ወአንትሙሰ ተዐቀቡ ወግበሩ ተዝካረ ሕማማቲሁ” የሚለውን የአበውን ትዕዛዝ አብነት በማድረግ የክርስቶስን  ሕማም የሚዘከርበት በዓል ነው፡፡ በኦርቶዶክሳውያን ዘንድ ታላቅ ቦታ ያለው እጅግ ልዩ የሆነ ድባብ የሚፈጥር ሊቁ ዪሐንስ አፈወርቅ “ይትባረክ እግዚአብሔር ዘሰመየ ሕማማተ ወልዱ ክቡረ ወስብሐተ”ያለለት በሕማም እና ድካም በአልፎ በታላቅ ፍስሐ እና ሐሴት የሚደመደም በዓል ነው ፡፡ስንዱዋ እመቤትም ይህንን በዓል መሰረት አድርጋ ወንጌልን ገልጣ፣ ስለዚህ ሰማያዊ ምስጢር ፣ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የጥል ግርግዳን እንዳፈረሰ ፣ በደሙ ፈሳሽነነት የሰውን ልጅ እንደታደገው ታስተምራለች፡፡ትላንት፣ ጥንት ፣ ከሁለት ሺሕ አመታት በፊት ሳይሆን ዮም ተሰቅለ፤ ዮም ተንስኣ፤ እያለች፡፡ኢየሱስም ያደረገው ብዙ ሌላ ነገር ደግሞ አለ፤ ሁሉ በእያንዳንዱ ቢጻፍ ለተጻፉት መጻሕፍት ዓለም ራሱ ባልበቃቸውም ነበር እንዳለ ወንጌላዊው ተነግሮ አያልቅም፡፡እኔ ግን ሁሌም በዚህ ሰሞን እጅግ የሚገርመኝ የሊቃውንቱ የተመስጦ ማጠንጠኛ የሆነችው በጦማራችን መጀመሪያ ላይ ያለችው ሐረግ ናት፡፡
      በምሴተ ሐሙስ ሊቃውንቱ በታላቅ ተመስጦ ሆነው ደጋግመው ይሉታል፡፡የኔ ቢጤ ጨዋ እንኳ በቀላሉ ቃላቶቹን ይለያቸዋል፡፡ዜማው ልብን ሰርስሮ ሲገባ፣ ጠና ያሉ አባቶች ከእንባቸው  ጋር እየታገሉ ፣  ሳግ እየቀላቀሉ ሲያሄዱት እንዴት አንጀት ያኝካል መሰላችኹ፡፡ ሊቀ መዘምር ይልማ ኀይሉ “ኢየሱስም አለ” በተሰኘችው የመንፈስ ፍሬው ዜማውን ከነመልዕክቱ ለማድረስ ያደረገው ጥረት ይበል የሚያሰኝ ነው፡፡

     ወደ መልዕክቱ እንግባ፡፡ያው እንደሚታወቀው ለኛ ለኢትዮጵያውያን ጭቆና አዲስ ነገር አይደለም ታላቅ ወንድም ይጨቁነናል ፤ ወላጅ ይጨቁነናል፤የክፍል አለቃ ይጨቁነናል፤ መምህር ይጨቁነናል፤ የሰፈር ጉልቤ ይጨቁነናል፤የቀበሌ ሹም ይጨቁነናል፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ይጨቁነናል… የሚገርመው ብዙዎቻችን ይህንን እንደ ኮሶ የተጣባንን መጨቋቆን ስንቃወም እንታያለን፡፡ ነገር ግን የጩኸታችን ምክንያት እኛ ከላይ ባለመሆናችን ብቻ ነው ፡፡
      ታዲያ ለዚህ ህዝብ ነው ከበድ ያለ መልዕክት የደረሰው  “እግረ አርዳኢሁ ሐፀበ” የረድ አገልጋይን እግር ማጠብ እንኳን እኛ ለሐዋርያው ጴጥሮስ እጅግ እንደከበደች  መጽሐፍ እንዲህ ብሎ ይነግረናል፡፡ “ከእራት ተነሣ ልብሱንም አኖረ፥ ማበሻም ጨርቅ ወስዶ ታጠቀ፤በኋላም በመታጠቢያው ውኃ ጨመረ፥ የደቀ መዛሙርቱንም እግር ሊያጥብና በታጠቀበትም ማበሻ ጨርቅ ሊያብስ ጀመረ።ወደ ስምዖን ጴጥሮስም መጣ፤ እርሱም፦ ጌታ ሆይ፥ አንተ የእኔን እግር ታጥባለህን? አለው።”ይህ ነው ሊቃውንቱን ያነሆለላቸው፤ ነፋሳቸውን ሰቅዞ የያዘው፡፡ ምክንያቱም አይሁድ በዚያን ጊዜ እንደኛ ህዝብ በቀቢጸ ተስፋ የተያዙ ፣ የቄሳሮች የጭቆና ቀንበር ያደቀቃቸው ፣ ማኀበራዊ ቀውስ የነገሰባቸው ነበሩ ልክ እንደኛ፡፡
      ቅዱስ ጴጥሮስ የከበደው የአምላኩ የመምህሩ ጎንበስ ብሎ እግር ማጠብ ብቻ አይደለም(እርግጥ እርሱም ታላቅ ምስጢር ነው) የነበረው ስርዓት ደንብ መፍረሱም እንጂ፡፡ ገዥ እና ተገዥ ፣ አለቃ እና ምንዝር  ፣ ሕዝብ ና መንግስት ባሪያና አሳዳሪ የሚለውን ስርዓት ማፍረሱ ነው፡፡ለዚሀም ነው ሊቃውንቱ ደግመው ደጋግመው የሚጮሁት ፤ ከባዱን ነገር ነገር ለማፍረስ እራስን ዝቅ ማድረግ ፤ እውነት  ነው! ለዚህ አንክሮ ይገባል ፡፡የማይሆነው ሲሆን አንክሮ ይገባል፡፡ ለዚህም ጌታችን እንዲያስተውሉት በአጽንኦት የነገራቸው፡፡ “…ያደረግሁላችሁን ታስተውላላችሁን?…”አንትሙኒ ከመዝ ግበሩ፡፡ለቢጽክሙ፡፡ለወንድሞቻችሁ እንዲሁ አድርጉ እኔ እንደእናትም እንደ አባትም እንደሆንኩላችሁ እናንተም ለወንድሞቻችሁ እንዲሁ እድርጉ፡፡ልብን ጭልጥ አድርጎ የሚያነጉድ፡፡ ሐዋሪያቲሁ ክበበ….

ስደት በየፈርጁ፥ በአካል፣ በቅዠት፣ በሆድ፣ በመንፈስ ፣ በትዕቢት

Standard
          የእስልምና እምነት መሰረታዊ ትዕዛዛት እንዱ የሆነው ወደመካ መዲና የሚደረገው ሐጅ  እንዲሁም ኢትዮጵያውያን መነኮሳት የግብጽ በረሃዎችን አቋርጠው ወደ ቅድስት አገር ኢየሩሳሌም የሚያደርጉት ጉዞ ቀደም ላለው የኢትዮጵያውያን ከሀገር የመውጣት ታሪክ መነሻ ይሆነናል፡፡ከዚያ በኃላ በሀያኛው ክፍለ ዘመን መባቻ ጀምሮ ኢትዮጵያውያን ወጣቶች ወደሌሎች ሀገራት ተጉዘው እንደነበረ የታወቀ ነው፡፡እንደውም የበረቱት ሄድውበት የነበረው ሀገር ከኛ ማኀበረሰብ ጋር አወዳድረው “በዚህ በዚህ ወደኃላ ቀርተናል ፤ እኛ ከእነርሱ በዚህ እንለያለን፡፡” የሚሉ ድርሳናትን ትተውልን አልፈዋል፡፡ታላቁ የስነ ማኀበረሰብ ጥናት ሊቅና በኢትዮጵያ ጉዳዮች ሁሉን አወቅ (expert) የሆኑት ዶናልድ ሌቪን የእሊህን(ከ1876- 1922 እ.ኤ.አ. ከሀገር የወጡትን) ቁጥር በድፍረት 35 ናቸው ይሉናል፡፡
           Continue reading

ወንድ ያቀፈ ወንድ

Standard

    …በውስጥ ግዛት ከግዛት ሳይለይ አጠቃላይ አመጽ ተነሣበት፡፡ በውጭም ቢሆን እርዱኝ ብሎ እጁን ከዘረጋላቸው አውሮጳውያን ያገኘው መልስ ዝምታ ወይም ንቀት ብቻ ነበር፡፡ከጭንቀትና ከመከፋት የተነሣ ጭካኔን መፍትሔ አድርጎ ያዘው ፡፡ጠላቱንና ወዳጁን መለየት አልቻልም፡፡ሁሉም ላይ የቁጣውን መቅሰፍት እኩል አወረደባቸው፡፡ ይህም ሁኔታውን አባባሰው፡፡በውስጥ ጠላቶቹን ይበልጥ አበራከተበት ፤ በውጭ ደግሞ ለፍቅርና ለወዳጅነት ደብዳቤዎቹ ደንታ ያልሰጡትን እንግሊዞች አስነሣበት፡፡ሊረዱት ያልተዘጋጁት ሊያጠፉት ተነሡ…



በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አንድ አምላክ በሶስትነት ባንድነቱ በክርስቶስ ያመነው ካሳ መቸም  ያገሬ ሰዎች በእግዚአብሔር ኃይል እኔ ካልወረድሁላችኹ ሽሽታችኹን አትተውም፡፡ክርስቲያኑን ሁሉ ጉልበት አለኝ መስሎኝ ካረመኔ አገር አግብቼው ወንድ የሌላት ቆንጆ አለች ወንድ የነበራት ቆንጆ ነበረች ትላንትም የሞተባት ትኖራለች ሽማግሌ ልጅ የሌለው ባልቴት ልጅ የሌላት እኔ እኔ የምጠውራቸው ብዙ በከተማየ አሉ ፡፡እግዚአብሔር ከሠጣችሁ ፍቀዱኣቸው ያረመኔ አገር ነውና ያገሬ ሰው ገብር ሥራት ግባ ብዬ ብለው እምቢ ብሎ ተጣላኝ፡፡እናንተ ግን በስራት በተገዛ ሰው አቸነፋችሁኝ፡፡እኔን ወደውኝ የተከተሉኝ ሰዎች አንድ እርሳስ ፈርተው ጥለውኝ ሸሹ ብትቃጧቸው ከሮጡ ሰዎች ጋራ አልነበርሁም ጌታነኝ መስሎኝ ባልሰላ መድፍ ሥታገል ውዬ ነው፡፡ ያገሬ ሰው የፈረንጅ ሃይማኖት ይዞአል አስልሞአል እያለ አስሩን ምክንያት ይሰጠኝ ነበረ፡፡ እኔ ከከፋሁበት እግዚአብሔር መልካም ይሠጠው  እንደወደደ ይሁን እግዚአብሔር ቢሠጠኝ ሁሉን ልገዛ አሳብ ነበረብኝ፡፡እግዚአብሔር ቢነሣኝ ልሞት አሣቤ ይህ ነበረ፡፡ከተወለድሁኝ እስታሁን ወንድ እጄን ጨብጦት አያውቅም ነበረ ሰዎች ሢሼሹ ተነስቼ ማራጋት ልማድ ነበረኝ ጨለማ ከለከለኝ፡፡ትላንትና በደስታ ያደራችሁ ሰዎች እግዚአብሔር እንደኔ አያድርጋችሁ፡፡እንኳን የሀበሻ ጠላቴን ኢየሩሳሌም ዘምቼ ቱርኮችን አስለቅቃለወሁ መስሎኝ ነበር፡፡ ወንድ ያቀፈ ወንድ ተመልሶ አይታቀፍም፡፡
(Rubenson,acta ii,354)
       …ይህ ደብዳቤ ፍጹም ቴዎድሮሳዊ የሆነ የእድኔ ልክ ህልሙንና ጥረቱን ያካተተ የታሪክ ሰነድ ነው ለእንግሊዛዊው ጄኔራል ይጻፍ እንጂ መልዕክቱ ለሀገሬው ህዝብ ነው፡፡ አልገዛ ላለው ህዝብ የሟች ወቀሳ ነው፡፡ ለደካሞች ያለውን ርኅራኄና ኢየሩሳሌምን ነፃ አወጣለው ብሎ የተነሣበት ዓላማ ሲከሽፍበት የተሰማውን ጸጸት ያጣመረ ሰነድ ነው፡፡
 (በሚያዝያ 3፣ 1860 አጼ ቴዎድሮስ ለባለድሉ ጄኔራል ናፒየር የጻፈውን ደብዳቤ  መሰረት አድርገው የታሪክ ምሁሩ ባሕሩ ዘውዴ “የኢትዮጵያ ታሪክ ከ1847 እሰከ 1983 ፣ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬስ ፣ 2003”  በታተመው መጽሐፋቸው እንዳተቱት)