ከፌዝቡክ ውጣ ወደ ፌስቡክ ግባ

Standard

Log out from ‘fazebook’ but log in to facebook 

        በቅርቡ አምስተኛ አመቷን ባከበረችው በአዲስ ጉዳይ(ሮዝ) መጽሔት ሁለት ተከታታይ እትሞች “ፌስቡክ ከወሲብ ገበያ እስከ አብዮት” የሚል ረጅም  ጽሑፍ አነበብኩኝ:: ጽሁፉ እና እኔ የማውቀው ፌስቡክ አልተገናኝቶም ሆኑብኝ፡፡ ከዚያም ለዚህ ፌስቡክን የማያውቅ ፌስቡካዊ ጽሑፍ ምላሽ የምትሆን አጭር መጣጥፍ ለመጣፍም ዳዳኝ፡፡ የመጀመሪያው በርዕሱ ስለጠቀሰው አብዮት እዚህ ግባ የሚባል ዳሰሳ አልቀረበም፡፡  ከዚህ በተጨማሪም ፌስቡክ አመጣሽ ችግር መከላከያው ምን አንደሆነ አልጠቆመንም ወይንም ፌስቡክን እንዴት ባግባቡ መጠቀም እንዳለብን ምከር ቢጤም የለውም፡፡


          በአንድ መንግስታዊ ድርጅት ከሚሰራ ወዳጄ ጋር በዚህ እና ሌሎች ተዛማጅ ጉዳዮች ላይ ስንጨዋወት በመስሪያ ቤቱ ያለበትን ብሶት አጫወተኝ፡፡ እንደ እርሱ አለቆች ግንዛቤ ፌስቡክ መጠቀም የዋልጌዎች ስራ ነው፡፡ በስራው ወዳድነቱ እና በጥሩ ስነ ምግባሩ የሚወዱት አለቆች ሳይቀር ፌስቡክ ገጹ ላይ ተስጥቶ አግኝተውት “አንተም ተበላሸህ?” በማለት እንዳዘኑበት ገልጾልኛል፡፡ ይህ የወዳጄ ሮሮ እንዲሁም የአዲስ ጉዳይ መጽሔት ዘገባ የአቻዎቼን የፌስቡክ ውሎ እንድመረምር አስገደደኝ፡፡ እንዲህም ሆኖ አገኘሁት፡፡   
        ብዙዎቻችን ማለት ይቻላል ጊዜያችንን የምናጠፋው የቆነጃጅትን ፎቶዎች በማየት ነው፡፡ ከዚያም ልጅት ከፈቀደች add በማድረግ፣ እዚህ ግባ የማይባል የእንቶ ፈንቶ chat በማድረግ ነው ፤ በአጠቃላይ digital ድድ ማስጫ አድርገነዋል፡፡ሴት እህቶቻችንም ልዩ ክስተቶችን ቀርጾ ከማሰቀመጥ በዘለለ ለገበያ እንደቀረበ ሸቀጥ ወይንም FBI እንደያዘው ተጠርጣሪ ከተለያየ ማዕዘን በመነሳት የፌዝቡከሮችን ቀልብ ለመሳብ ጥረት ያደርጋሉ፡፡ በዚህም ምክንያት ወግ አጥባቂ አለቆቻችን ቀርቶ ሌላው በጎ አሳቢ ሊቀላቀለን ፍቃደኛ አልሆነም፡፡የአለቃና ምንዝር ግንኙነትን ለጊዜው ወደጎን ተወት አድርገነው ፊደል ቀመስ ወላጆቻችን እንኳን ይህንን ጉዳይ በበጎ ይመለከቱታል ለማለት ይከብዳል፡፡የተለመደው በቤት ያለ አልበም እንኳን አቧራው የሚራገፈው ቆየት ያለ ወዳጅችንን ቤት ለእንግዳ ያልን እንደሆነ ነው፡፡ፌስቡካዊው ወዳጄ ታምራት ታም ራት ይህንን ወለፈንድ የሚገልጽ አጭር   እንካ ሰላንቲያ(chat) ፌስቡክ ግርግዳው ላይ ለጥፎ ሁላችንንም የምር ጥርሳችንን አስከፍቶናል፡፡ በሞቴ ሳቄን ላካፍላችኹ ቢያንስ ፈገግ እንኳ  በሉልኝ፡፡
Titi: yene konjoooooooooooooooooooo

Bety: Weyeeeeeee sitamri eko 

Titi: ♥♥♥ tnx kanchi balbeltim ♥♥♥

Bety: eeeeeeeee mozaza lol 

Titi ♥♥lol♥♥

Bety: bettam Qonjo nesh Eshi? 

Titi: lol thanks lol ahun wede bet lihed new lol 
Abebe: Lol 
Bety: bye ♥♥♥ lol

        
         ይህን ነገር የሚጋሩት ቴክኖሎጂውን በሩቁ የሚመልከቱት ብቻ አይደሉም፡፡እኛን ፌስቡካወያንን ተቀላቅለው ያቀማቸውን አስተዉለው   በዋዛ ፈዛዛ ጊዜያችንን ከምናሳልፍ በማለት ገጻቸውን deactivated አድርገው የፈረጠጡም ይገኙበታል፡፡የፌስቡክ አትጠቀም እጠቀማለው እሰጥ አገባ መነሻም ከዚህ ይመነጫል፡፡ ወዳጆቻችን በፌስቡክ ስንባዝን እንጂ ስንጠቀም አላገኙንም ፡፡ የማርክ ዙከርበርግን ፌስቡክ አያወቁትም፡፡ፌስቡክ ያለው ሌላ እኛ የምንጠቀመው ሌላ፡፡ አንዳንድ ሞያዎች ባለሙያ ነን የሚሉ ሰዎች ሀገሪቱን አጨናንቀዋት እያለ ሙያው ወደሀገራችን አልገባም እንደሚባለው ፌስቡክንም መጠቀም የጀመረን አልመሰለኝም ፡፡
         እንደኔ እንደኔ እኛ እየተጠቀምን ያለነው ፌስቡክ ሳይሆን ፌዝቡክን ነው፡፡ከባሪያይቱ አንዱም ከጨዋይቱ ደግሞ ሌላ በድምሩ ሁለት ልጆች ለአብርሃም እንደ ነበሩት በታላቁ መጽሐፍ እንደተጣፈ ለማርክዙከርበርግ ሁለት ልጆች አሉት ፌስቡክ የጨዋይቱ ፤ ፈዝቡክ የባሪያይቱ፡፡ ፌስቡካውያን የጠፋ ወዳጅ ፣ ዘመድ ይፈልጉበታል፤ ከእነርሱ የበለጠ የሀሳብ ልዕልና ያላቸውን ሰዎች ፈልገው ያወጉበታል፡፡በሌሎች መካነ ድር ያገኙትን የማረካቸውን ለወዳጆቻቸው ያካፍሉበታል ፡፡የፈዝቡክ ተጠቃሚዎች ደግሞ በተቃራኒው እራሳቸውን በስም እና በምስል ደብቀው የጽንፍ ቦለቲካቸውን ያራምዳሉ ወይንም መረን በለቀቀ ብልግናቸው የንጹሓንን የፌስቡክ ገጽ ያቆሽሻሉ፡፡
          እንግሊዘኛ እና ህልም እንደ ፈቺው ነው ብለን  በስልታዊ መላ አለማወቃችንን ብንሸፍንም ጭራ ከሆንባቸው ጉዳዮች አንዱ እንግሊዘኛ ቋንቋን አቀላጥፎ መናገር ነው:: እንግሊዘኛ ቋንቋ በታላቋ ብሪታኒያ ተወልደ፤ በአሜሪካ አደገ፤ ህንድ ታመመ፤  አፍሪካ (አትዮጵያ) ሲደርስ ሞተ የሚል መነሻው የማን እንደሆነ ለጊዜው ያልደረስኩበት አባባል አለ፡፡  እንግሊዘኛ ማወቅ የምሑርነት ምልከት ነው እያልኩ እንዳልሆነ ተረዱልኝ፡፡ነገር ግን በኔ በጥናት ያልተደገፈ ንቁ ተመልካች(active audience) በመሆን ብቻ በተወሰደ  ግምት ከእንግሊዘኛ ይልቅ ፌስቡክን በመግደል የሚያሰከስሰን ይመስለኛል፡፡ ለምን ብትሉኝ ከፈርጀ ብዙ ጥቅሞቹ መቋደስን ትተን በአልባሌው ላይ ማተኮራችን ነው፡፡ በንቃተ ህሊና ከብዙዎቹ የአለማችን ህዝቦች አንድ ጋት የራቁ ናቸው ተብለው የሚታሙት አረቦች እንኳ በአግባቡ ተጠቅመውበት  የሰው ልጆች ከጭቆና እና ጨቋኞች ጋር የሚያደርገውን የማያልቀውን ትግል ብዙ የስኬት ምዕራፍ እንዲጓዝ አስችለውታል፡፡ታዲያ እኛስ እንደ ፈርኦኖች ሀገር ሰዎች ባይሆን እንኳ በመጠኑ መግባባታችንን የሚጨምር ረብ ያለው ነገር መከወን ሊያቅተን አይገባም፡፡  ሁሉም ነገር በመላ ካልተያዘ ከጥቅሞቹ ጋር ጉዳቶችን ትቶልን ይሄዳል፡፡የእናቶቻችን ቡና ጠጡ እንኳ ለሐሜት ይጋለጣል፡፡ለዚህም ነው አሳን መብላት በብልሃት የምንለው፤ ነገር ግን ፌስቡከ ላይ ይህ ብላሃታችን አልታየም፡፡ ከጨዋይቱ ይልቅ ባርያይቱን ልጅ መምረጣችን የዘመኑን ጥበብ ባግባቡ እንዳንጠቀም አድርጎናል፡፡
      ይህንን ክፍተት የሚሞሉ “የሀገር ሰዎች” እጥረት የኢትዮጵያዉያን ውሎ በፌስቡክን ከፊል ደመናማ እንዲሆን አድርጎታል፡፡በጨቋኞች የተከለከልነው ብሔራዊ እርቅ እና ሀገራዊ መግባባትን ለመፍጠር ወይም የበኩላችንን ድርሻ ለመወጣት የግድ ሊቅ መሆን አይጠበቅብንም፡፡በግብጽ አስራ አብድልፈታህ የተባለች የ27 ዓመት ወጣት ናት የፈስቡክ ግሩፕ አቋቁማ  ለአብዮቱ  መነቃቃት ከፍተኛ አስተዋጽማበርከት የቻለችው፡፡
           ፌስቡክ እና መሰሎቹ የማሕበራዊ ትይይዝቶች ከሌሎች መካነ ድሮች በተለየ ብዙ ጥቅሞችን ይሰጣሉ፡፡ የመጀመሪያው በከፊል ወይም ሙሉ በሙሉ ለህዝብ እና ለአህዛብ  ክፍት የሆነ ውስን ገጸ ርዕይ (profile) መክፈት ማስቻሉ ነው፡፡በዚህም መሰረት ከልጅነት እስከ እውቀት የሄድንበት መንገድ ፣ ከፊደል ቆጠራ እስከ ከፍተኛ ትምህርት የገበየንባቸው ተቋማት፣ ተቀጥረን የሰራንበት መስሪያ ቤት ፣ ከሀይማኖት እሰከ ቦለቲካዊ አቋማችንን የምናሰፍርበት በአጭር ጽሑፍ እና ምስል አስደግፈን ማቅረብ የምንችልበት ምህዳር አላቸው፡፡ ሁለተኛው ከሌሎች ተጠቃሚዎች ጋር የሚያገናኛቸው ትይይዝት መፍጠር መቻላቸው ነው፡፡ጓደኛና ወዳጅ በፌስቡክ በሽ በሽ ናቸው፡፡ ጊዜ ና ቦታ ሳይግደን የልብ የልባችንን ማዉጋት እንችላለን፡፡ከሌሎች መካነ ድሮች ያገኘናቸውን መረጃዎች(text, image and video) ለወዳጆቻችን በቀላሉ ማጋራት እንችላለን፡፡እነርሱስ ምን ሊግሩን ፈልገዋል የሚለውን ከገጻቸው ማግኘታችን ደግሞ ሰናይ ነው፡፡አይተን ብቻ አናበቃም፤ ወድጄዋለው (like) ከማለት በዘለለ በጉዳዩ ላይ አስተያየት መስጠት መቻላችን ከሌሎች ሰዎችም እሺ እንዴት አየኸው ብለንም መጠየቃችን ተወዳጅ እንዲሆኑ አድርጓቸዋል፡፡
      ፌስቡክ እንደ ኢትዮጵያ ላሉ ሀገሮች ቅንጦት አይደለም፡፡ማንኛውም ሰው ያለ ማንም ጣልቃ ገብነት ሀሳብን የመግለጽ ነፃነት አለው የሚል ልፈፋን ለረጅም ጊዜ ብናደምጥም እውነታው ከዚህ የተለየ ነው፡፡ሌላው ቢቀር በቅርቡ በሽብርተኝነት የተከሰሱት ባረጀ ታፔላ ላይ በቃ!!! የሚል ጽሑፍ ልትጽፉ ወይም ልታጽፉ ስትመክሩ ተገኛችሁ በሚል ነው፡፡ የሚገርመው ህግን ለአመታት በከፍተኛ ተቋማት ያጠኑ ሰዎች ይህንን ለማውጣጣት የምስክር ጋጋታን ሲያደምጡ መክረማቸው ነው፡፡በማርያም!!! አሁን ይሄ በሽብርተኝነት ሊያሰከስስ ቀርቶ ግማሽ ቀን ወህኒ ያውላል?
      በእንዲህ ያለ አይን ያወጣ ሽበባ ውስጥ በመኖራችን ነው  ፌስቡክን እና ሌሎች መሰል ማኀበራዊ መካነ ድሮችን የሙጢኝ ማለት ያሰፈለገን፡፡ሌሎቹ መንገዶች ብዙም ላያዛልቁን እንደማይችሉ የሚዲያዎቻችንን ጥንካሬ እና ብስለት መመልከቱ ወደ ተስፋ መቁረጥ ይመራናል፡፡ አሁን አረጁ አፈጁ የሚባሉትን ሚዲያዎች ትተን እንደማሳያ የጡመራን(blogging) ብናነሳ ቀድሞ የተገነባ ጭፍን ደጋፊ  (blind supporter) እና አሻሚ ፣ አደናጋሪ ስምን (fuzzy cult) ይጠይቃሉ ፡፡ በዚህም ምክንያት ከህዝባዊነት ይልቅ ቀድሞ የተገነባ የግለሰቦች ማንነት ሀሳብን ያንጸባርቃሉ፡፡የሚያካፍሉን ሀሳብ ከጀርባ ሌላ አጀንዳን እንዳላዘለ ማረጋገጥ ይከብደናል፡፡
              ከታሪክ እንደተማርነው በየአዝማናቱ የነበሩ ክስተቶችን የተወሰኑ ሰዎች ወደፈለጉት አቅጣጫ ይመሯቸዋል(ለእኩይ ወይም በጎ ሊሆን ይችላል) በዚህም ምክንያት ወደድንም ጠላንም በሰው ዘር ላይ የራሳቸውን አሻራ ማሳረፋቸው የማይቀር ነው፡፡ ይህንን የዘመን ጎርፍ ገድቦ ማስቀረት አይቻልም፡፡ ይልቅ የሚበጀው ወገብን ጠበቅ አድርጎ በወግ በወጉ ለሰናይ ምግባራት እንዲውል መግራት ነው፡፡ፌስቡክም ይህንን እየጠየቀን ነው፡፡እኔ የተመለከተኳቸውን ጥቂት ነጥቦች በማንሳት ላብቃ፡፡
         የመጀመሪያው በገሀዱ አለም ያለው ማንነታቸችን እና በኢንተርኔቱ ዓለም የገነባነው ማንነት (cyber identity) ወደአሀድነት እያመሩ ነው፡፡ ስለዚህ በፌስቡክ እና ሌሎች መሰል ማኀበራዊ ትይይዝቶች ላይ ያለን እንቅስቃሴ እስኪገባን ድረስ ቁጥብ ፣ በኃላ ደግሞ ጥንቃቄን ከብስለት ጋር አጣምሮ የያዘ መሆን ይገባዋል፡፡የመካነ ድሮቹ ባለንብረቶችም ተኝተው አያድሩም፡፡ የግለሰቦችን ግላዊ ኑሮ እና ፍላጎት ላለመጋፋት የተለያዩ ስልቶችን ይቀይሳሉ፡፡(account and privacy setting)እነዚህን ለመረዳት ማስተዋል ፣ የተሻለ ተጋላጭነት(exposure) ያላቸውን ሰዎች ማማከር፣ ሰዎች ሲያዩኝ እንዴት ነኝ ማለት ያስፈልጋል፡፡(view as… in facebook) በመቀጠል   ከሳይበር ወዳጆቻችን ጋር ያለን ግንኙነት በበኩሌ ኢትዮጲያዊ ጨዋነትን የተላበሰ ቢሆን እመርጣለው፡፡ይህንን ተፋልሶ  በአዲስ ጉዳይ መጽሔት በሰፊው ያገኙታልና መድገም አያስፈልግም፡፡ መተዋወቁ፣ መወያየቱ እና በጋራ የምንወዳቸውን ነገሮች መለዋወጡን በክፉ ማየትን እቃወማለው፡፡ ከዚህ ያለፈ ወዳጅነት ካሻን ግን ነገሩን ከአየር ወደመሬት አውርደን እንደ ባለአእመሮ መነጋገር መልካም ነው፡፡
        ሌላው ምክክር የሚያሻው ጉዳይ በዚህ አገዛዝ ላይ ያለን   ቅዋሜ (antipathy to the regime)ነው፡፡ እርግጥ ነው ብዙዎቻችን የሀገራችን ችግር እና ችጋር አንገሽግሾናል፡፡በዚህም ከ facebook status update አንስቶ በተለያየ መንገድ ለሀገራችን መቸገር የአንበሳውን ድርሻ የሚይዘው የአቶ መለስ አስተዳደርን በቃህ እያልን ነው፡፡ ሰናይ ነው፡፡ እንደኔ ግን በጭፍኑ በቃህ ብሎ የቁራ ጩኸት ማሰማት መፍትሔ አይመሰለኝም፡፡ ብሔራዊ እርቅ እና ሀገራዊ መግባባትን ለማምጣት ቀድመው የበሰሉ እና የበለጸጉ የሳይንስ እና ፍልስፍና መርሖችን ከሀገራችን ሀይማኖቶች እንዲል (saying) ጋር በማቆራኘት ምን ይሻለናልን መጮህ፣ መስራት ይገባናል፡፡የሰው ልጆች የምድሪቱን ፍሬ በፍትህአዊነት ተካፍለው በፍቅር በሰላም በበጎ ሁኔታ እንዴት መኖር አለባቸው የሚለውን ለዘመናት የተካሄደ ተዋስኦ(discourse) በልካችን መስፋቱ የሚቀድም ይመስለኛል፡፡ እኔ “ሰውየው ምሁር ነው! ከእርሱ በላይ ሊቅ ከየት ሊመጣ? ተቃዋሚዎችን ተመልከቷቸው እርስ በርስ እንዴት እንደሚናከሱ!!!” ከሚሉት ወገን አይደለሁም፡፡ እርሱ ሀገሪቱን ቁልቁል የኋሊት እንደነዳት ማንም ይህን ማድረግ አያቅተውም፡፡ በፌስቡክ  440,080 ያህል ኢትዮጵያውያን ይገኛሉ፡፡ ቢያንስ እኛ እንኳን በመሰረታዊ የመጪው ጊዜ ጉዳዮች ላይ መግባባት ይጠበቅብናል፡፡
       እውነተኛ ለውጥ፣ የማይቀለበስ ሰላም Facebook revolution, Twitter revolution, Revolution 2.0 በማለት፣ ይህን ደጋግሞ በማዜም፣ ስምን ደብቆ(by being anonymous) እንታገል፣ ቁረጠው፣ ፍለጠው በማለት አይመጣም፡፡ፌስቡክ አብዮት አዳዲሰ የፈጠራ መታገያ ስልቶችን፣ ራስን መቆጣጠርን  እና ስነ ምግባርን ይጠይቃል፡፡ በመገ’ለጥ ሀሳብን ደግሞ ተንትኖ በመግለጥ እንጂ ተደብቆ ተራ ስድብን በመደርደር አይገኝም፡፡ የረጅም ጊዜ ውጤታማ ለውጥ እኛ ፌስቡክ ላይ ስለለጠፍን ሁሉን ነገር twit ስላደረግን አይመጣም፡፡የምንሰጠው መረጃ ይህን ለውጥ ፈላጊ ሀይል የሚያበረታ፣ የሚያጀግን ፣ የሚያነቃቃ፣ ልብን ስለፍትህ፣ ስለሰላም ፣ስለእኩልነት ፣  እንድትቃትት የሚያደርግ መሆን አለበት፡፡
    ሌላው መታሰብ ያለበት ማኀበረሰባዊ ሚዲያ (social media) ቢሮ የለውም፡፡ ሉአላዊነት እንዲሁ፡፡ ይህ ደግሞ የሚጠቀማቸውን ነገሮች ነፃ ራሳቸውን የቻሉ እንዳይሆኑ አድርጓቸዋል፡፡በዚህም ምክንያት ትግሉ የሚካሄድበት ምህዳር በሌሎች ቁጥጥር ስር ነው፡፡እነዚህ ተቃውሞ መሳሪያዎች (facebook, twitter and other social Medias) በቀላሉ ወደ መጨቆኛ መሳሪያነት ተለውጠው ለድካም የፈጠረኝ ብነግድ አይተርፈኝ እንዳንል እስጋለው፡፡ኢንተርኔት አለአግባብ ጥቅም ላይ ሊውል፣ ለሳንሱር ሊጋለጥ ወይንም ሙሉ በሙሉ ሊዘጋ የሚችል ነገር ነው፡፡ በግብጽ አብዮት ኢንተርኔቱ ቢዘጋባቸው በአጭር የጽሑፍ መልዕክት እና የሬድዮ መገናኛ በመጠቀም ሙባረክን ከስልጣን ማውረዱን ከዳር አድርሰዋል፡፡ቻይና በቢሊዮን የሚቆጠር ሕዘብ ይዛ 527,720 ብቻ ፌስቡክ ተጠቃሚ(ከዓለም 93ኛ)  ያላት  ስለተዘጋነው፡፡የእንግሊዝ መንግስት የስራ አጥ ወጣቶችን አመጽ ለማፈን ፌስቡክን እንደሚዘጋ የዛተው በቅርብ ጊዜ ነው፡የአሜሪካ ኮንግረስአዲስ የሳይበር ህግ ሊያወጣ መሆኑን የሰሙ በርካታ መካነ ድሮች በቀዳሚ ገጻቸው ተቃዉሟቸውን ከገለጹ የጥቂት ቀናት እድሜ ብቻ አለፋቸው፡፡አሁን ብዙ መካነ ድሮችን ከእናት ሀገር ሆኖ በቀጥታ ማየት አይቻልም፡፡በብሎግ ስፖት የታገዙት ሁሉም ጦማሮች ሰሞኑን ወደወገኖቻቸው (ወደታፈኑት) ሳይቀላቀሉ አልቀረም ፡፡ ፌስቡክን መዝጋት ለሽመልስ ከማል(shameless camel) እኛ የቤታችንን መብራት እንደምናጠፋው የቀለለ ነው፡፡ ከዚያ የአለቃውን  “ETV in Print” or “The Bereket Delusion” or“Berkleaks” or “Bereket and the Forty Thievesን ይዘን በቃላችን ማጥናት ነው፡፡ እስከዚያው ግን በአስተሳሰብ እንመንደግ ወርቃማው እድላችንን ፌስቡክን ትተን በፌዝቡክ አንጃጃል፡፡  ጄን ሻርፕ በብዙ ስራዎቹ አበክሮ እንደሚገልጸው አገዛዝ ጸንቶ የሚኖረው ባለው ሀይል፣ ነፍጥ እና ጭቆናው ሳይሆን በህዝቦች ለመጨ’ቆን በተዘጋጀ ልብ እና ፈቃድ ነው፡፡ወደሽ ከተዳፋሽ ቢረግጡሽ አይክፋሽ እንዲል የኛ ሰው፡፡ please Log out from ‘fazebook’ but log in to facebook  

ሰላም አልገባንም !?

Standard

  ከመ’ኤሌትሪክ በሩቅ እንሽሸው
በአንደበታችን አንነጋገረው
አታንሳው አታንሺው
ተዪው እንተወው
እንዳያዳምጠን ባለ ብዙ ጆሮው::
         በሰንበት ፣ በሰንበት ጠዋት ከእንቅልፌ ተነስቼ ከታላቁ አንዋር መስጊድ  አዛን ፣ ከደብረ አሚን ተክለ ሀይማኖት ኪዳን ስሰማ ነፍሴ ሀሴት ታደርጋለች፡፡ቀዳሽ ካህናቱ ከቤተልሄም ወደ ቤተ መቅደስ ሳይገቡ ለመድረስ እየተፋጠንኩኝ ስሔድ ብዙ ሰዎች በየአቅጣጫው ሲራኮቱ አያለው፡፡
የሁሉም ጉዳይ ለየቅል ነው፡፡ ግማሹ ለሸገር ‘ጤናማነት’ ፍሬሽ አትክልት ለማቅረብ ወደ መዲናችን አትክልት ተራ ሲጓዙ ከፊሉ ደግሞ አንደ የእምነቱና አጥቢያው ጸሎቱን  ሊያስታኩት ወደ ጎላ ሚካኤል ፣  በኒን መስኪድ ወይም ወደ ደብረ አሚን ያመራል፡፡ በአዘቦት ቀናት ተማሪዎች ቦርሳቸውን አንግተው በአቅማቸው ሲሪየስ ቦጭቀው ወደ ትምህርት ቤት፥ ሠራተኞቹ ደግሞ አንድ ፐርሰንቱ   በግል መኪናቸው፥ ዘጠና ዘጠኙ እኛ እንዲሁ  በአውቶቢስ ፣ በታክሲ ወደ ቢሯችን ስንሄድ የሰላምን ነፋስ ያለከልካይ እየማግን ነው፡፡ 
            እኛ እንደሰማነው እነዚህ ነገሮች በዘመነ ደርግ የማይታሰቡ ነበሩ፡፡ሰዐት እላፊ ፣ ቀይ ሽብር ፣ ነጭ ሽብር ፣ ወፌ ላላ ፣ አለም በቃኝ ዘግናኝ ነገሮች መሆናቸውን ከሰማናቸው ተረኮች ተረድተናል ፡፡ ሀገሪቷ እንዴት ያን ወቅት አልፋ እኛ እንደተገኘን ባይገባንም ፥ ያ ዘመን ተመልሶ እንዳይመጣ  አይናችንን ከእጃችን ጋር ወደ አምላካችን እናነሳለን፡፡
         ሰርቶ መግባት ፣ ዘርቶ መቃም ፣ ወልዶ መሳም ፣ የወለዱት አድጎ በማዕረግ ሲመረቅ ፣ በወግ ሲዳር ማየትን የመሰለ ምን አለ?  በበዓላት ቤተዘመድ ፣ ጎረቤት ፣ ተሰብስቦ መጫወት ፤ ጎረምሶች በአውራ ጎዳና ፣ በካምቦሎጆ ፣ በየማሳው ቆነጃጅት  በየካፍቴሪያው ፣ በየሲኒማው ፣ በየገበያው  ሲዝናኑ ከማየትን በቀር ምን ደስ ያሰኛል? ከሚዲያው በጎ በጎውን መስማትም ያማረ ወይን እንደቀመሰ ጎልማሳ ያደርጋል፡፡ ከሁሉም ግን አንደ ህፃናት ጨዋታና የአንገት ስር ሽታ የሚማርክ የለም ፡፡ ይህም የሰላምን ወጋ ከፍ ያደርገዋል፡፡  ሰላም መሠረታዊ ጉዳይ ነው፡፡ማኀበረሰባችንም የሰላምን ዋጋ ያውቃታል፡፡ በሰባዎቹ መጨረሻ አና ሰማንያዎቹ መጀመሪያ የተወለዱ ህፃናት ስም ሰላም እያለ ቢጠራ ሰላምን እጅግ መናፈቁን ያሳብቅበታል፡፡ ሰላም ሲኖር ሁሉ ነገር አለ፡፡ ሰርቶ ማደግ ፣ ነግዶ ማትረፍ ፣ አምኖ መጽደቅ ፣ ተምሮ መመረቅ … በጎ በጎው ሁሉ ከሰላም ጋር ያብራል ፤ ወይንም የሰላምን ድጋፍ ይሻል፡፡ከንጉስ ዳዊት ጋርም አብረን  ወረሰየ ሰላመ ለበሓውርትኪ ወአጸገበኪ ቄቅሐ ሥርናይ (በወሰንሽም ሰላምን አደረገ፥ የስንዴንም ስብ አጠገበሽ )የምንለው እነዚህን ስንመለከት ነው፡፡
           በዚህ ከባቢ አየር የምንኖር ሰዎች ይህችን ‘ሰላማችንን’ እንዳንነጠቅ እንፈልጋለን፡፡ አደፍራሾችንም በጽኑዕ እንቃወማለን፡፡ ስለድህነት ፣ ጠኔ ፣  ሰብዓዊ መብት ፣ የዜግነት መብት ፣ ስለ ምስኪን ገበሬዎች ፣ ስለስደተኛ ወገኖቻችን ፣  ስለሴተኛ አዳሪ እህቶቻችን ፣ ጎዳና ተዳዳሪ ወንድሞቻችን ፣  የባህር በር ፣ የዋጋ ንረት ፣ የኑሮ ውድነት ፣ ሀሳብን በነጻነት መግለጽ ፣ የህግ የበላይነት ፣ ዴሞክራሲ ፣ መልካም አስተዳደር ፣ ሙስና ፣ የትምህርት ጥራት ፣ የጤና መርሐ ግብር የመሳሰሉት ነገሮችን በማንሳት እንደ ኩሬ ውሃ የረጋውን ህይወታችንን አንዲበጠብጥ አንፈቅድለትም ፡፡ ጋዜጣውን አናነብም መካነ ድሩን አንከፍትም ፡፡ ደፈር ብሎ “ምነው?” ብሎ  የሚሞግት ሲመጣ “አቦ!!! ሰላሜን ስጠኝ” እንላለን፡፡
ሰላም ምንድን ነው ?
          Peace ወይም pacificism የተሰኘው ቃል ሰላምን ለመግለጽ በምሁራን ዘንድ ለመግባቢያነት የዋሉ ቃላት ናቸው፡፡መነሻቸው በማቴዎስ ወንጌል በተራራው ስብከት  የሚገኘው በግዕዝ ብፁዓን ገባርያነ ሰላም፣ በአማርኛ ዕርቅን የሚያደርጉ ብፁዓን ናቸው፣ በእንግሊዘኛው Blessed are the peacemakers  የተሰኘው ገጸ ንባብ ነው፡፡ ቃሉ በግሪክ eirenopoios( eirênê + poiesis = to make peace)  ሲሆን ወደ ላቲን ሲተረጎም  pacifici (paci + ficus = peacemaking) ሆኗል፡፡
         ማንም ጤናማ እና በጎ ህሊና ያለው ሰው ይህ ሰላሙ አንዲጠፋበት አይፈልግም፡፡ ፈላስፎች ፣ የሐይማኖት መሪዎች  ፣ ሳይቲስቶች  ብዙዎች ዋና ጉዳያቸው አድርገውታል ፡፡ታላላቆቹን ሳይንቲስቶች አልፍሬድ ኖቤል እና አልበርት አንስታይንን ጨምሮ ማርቲንሉተር ኪንግሊዮ ቶልስቶይቮልቴር ሩሶመኀተመ ጋንዲሄነሪ ዴቪድ ቴሮውበርትራንድ ሩሴልኢማኑኤል ካንትጆንራውልጄን ሻርፕዳላይ ላማ የተሰኙት ታላላቅ ሰዎች ከዚህ ተግባርን ከንደፈ ሀሳብ ጋር አጣምሮ ከያዘው ኀልዮት ጋር ስማቸው ተደጋግሞ ከሚነሱት ውስጥ ይመደባሉ፡፡ የአለም ታላላቅ እምነቶች የግሪክ ፈላስፎችን ጨምሮ የሰው ልጅ ሰላምን ፍጹም ለማድረግ እንዲሁም እርስ በርሱ አንዴት መኖር እንዳለበት  የተለያየ ንድፈ ሀሳብ ቀርጸዋል፡፡ ክርስቲያኖች አንቀጸ ብፁዓንን ጠቅሰው ስለሰላም ያላቸውን አቋም ሲያብራሩ ሒንዱዎች፣ ጂኖች እንዲሁን ቡድሒስቶች አሒምሳ (ahimsa) ወይም ነወጥ አልባነትን(non violence) እንደዋና የሞራል ህግ ያሰቀምጣሉ፡፡ ፕላቶም በበኩሉ  ሁላችንም አብዛኛውን የህይወታችንን ክፍል ፣ ምርጥ መርጡን ልናበረክትለት የሚገባው ለሰላም አንደሆነ ተናግሯል፡፡ ናዚ መራሹ ፋሲሽዚም ፣  አፓርታይድ ፣  የጥቁሮች መብት በሰሜን አሜሪካና የነ አልቃይዳ አለም አቀፍ ሽብርተኝነት ከሞላ ጎደል አለም በህብረት ካወገዛቸው የቅርብ ጊዜ ነውጦች ወስጥ ይመደባሉ፡፡


        ፓሲቪስም ጸረ ጦርነት አቋም  ከመያዝ አንስቶ  የሰው ልጆችን ሞት ወይም መገ’ደል ፈፅሞ እስከ ማውገዝ የደረሰ ቁርጠኝነትን ይጠይቃል፡፡መቻቻል፣ ትዕግስት፣ ርህራሔ፣ ይቅርታና ፍቅርን በማኅበረሰብ ውስጥ ለማስረጽ የሚደረግ ትግልን ይጨምራል፡፡ በአንዳንድ ሀገራት ወንጀለኛ እንኳን በሞት እንዳይቀጣ የሚደነግግ ህግ የሚወጣው ከዚህ በመነሳት ነው፡፡
      ታዲያ በዚህ ሂደት ውስጥ ጨቋኞች፣ እብሪተኞችና አምባገነኖች ይኖራሉ ፡፡ በሰላም መንቀሳቀስ፣ ሀሳብን በነጻነት መግለጽን የከለከሉ፤ የምድሪቱን ፍሬ በስግብግብነት ለብቻ የሚበሉ፤ ህዘብን ለረሀብ፣ ለእርዛት እና ስደት የዳረጉ ፤ ሰፋፊ ወህኒ ቤቶች የገነቡ ፤የሰብዓዊ መብት ረገጣ የሚያካሂዱ፤ ቅኝ ገዢዎችና እናውቅልሃለን ባዮች ፡፡ እነኚህን ደግሞ መታገል ያሰፈልጋል፡፡የትግሉ ስልት ደግሞ ሰለሰላም፣ ስለነውጥ እና የሰው ልጅን ስለመግደል ባለን አመለካከት ይወሰናል፡፡ ማርቲን ሉተር ኪንግ  “Journey to Nonviolence,”  በተሰኘው መጣጥፉ “ለነውጥ አልባነት እና ለሰው ልጆች ሰላም ያለን ቁርጠኝነት ከሰውነታችን የሚመነጨውን ውሳጣዊ ነውጥ ፣ የቁጣና የጥላቻ መንፈስ በማሸነፍ ፍቅር እና ራስን ለሌሎች መስጠትን ወደውስጣችን ከመትከል  ነው” ሲል አትቷል፡፡
    
     ስለ የሰው ልጆች  ሰላም ግድ ያላቸው ሰዎች ብዙ በማብሰልሰል በህዝቦች ከመካከል ሰላም እንዲህ ይፈጠራል በማለት አመክንዮአቸውን ያሰቀምጣሉ፡፡ የመጀመሪያው ራስን እንደ ባሪያ ለገዢዎች አሳልፎ በመስጠት ፤ እንዲገዙን ጉልበታችንን፣ ሀብት፣ ንብረታችነን እንዲበዘብዙ ከመፍቀድ ፤ አንጸራዊ ሰላምን እናገኛለን ከሚል ሞኛሞኝ አስተሳሰብ የመነጨ ነው፡፡‘‘ቀኝህን ለመታህ ግራህን ስጥ” ፤ “ስለሚያሳድዷችሁ ጸልዪ” የሚለውን የካድሬ ስብከት በማሰማት ህዝብ  ጨቋኞችን አንዲሸከም የተደረጉ ሙከራዎች  የቅርብ ጊዜ ትዝታዎች ናቸው፡፡ ይህ ደግሞ ወሰን ወደሌለው ኢፍትሃዊት ያመራናል፡፡ መመህር የኔሰው ገብሬ እና ቱኒዚያዊው ሙሐመድ ቡአዚዚ እንደፈጸሙት ፓትሪክ ሄነሪ  “ነፃነቴን ስጡኝ ወይም ኑዛዜዬን ተቀበሉኝ”  በማለት እንደጠየቀው  አይነት ነገር ይከሰታል፡፡
          ሁለተኛው ሁለት ተጻራሪ ሀይሎች አንዱ አንዱን በመፍራት ጥላቻ እና ጸብ እንዳለ ሆኖ አንፃራዊ እና ጊዜያዊ ሰላም ይገኛል ብለው  ያመናሉ፡፡ እንደ ማስረጃም ከሁለተኛው ጦርነት በኃላ በቀዝቃዛው ጦርነት ጊዜ በአሜሪካ እና በሶቪየት ህብረት መካከል የነበረው መፋጠጥ ነገር ግን አለመታኮስን ያነሳሉ፡፡ ብዙዎቹ አማናዊ ሰላም ናፋቂዎች ግን በዚህ አይስማሙም፡፡ ለአጽንኦተ ነገር ታላቁ ፋላስፋ ኢማኑኤል ካንት “ሰላም፥ የሁሉም አለመግባባቶች እና ቅራኔዎች ፍጻሜ ነው” በማለት የተናገረውን ይጠቅሳሉ፡፡ በተለይ እንደኛ ባሉ ሀገራት በጨቋኝ አምባገኖች እና በህዘብ መካከል የሀይል ሚዛን መተካከል ስለማይኖር  ሰላም የማይታሰብ ነው፡፡
    
           ሶስተኛው ሊበራል ዲሞክራቶች የሚያቀንቀኑት ሲሆን ፍትሕን ለማሰፈን በሚደረጉ ጦርነቶች ሀገሮችን ወደማይቀለበስ ሰላም ያመጣቸዋል:: በዚህም መሰረት ዴምክራሴያዊ መንግስት ይገነባሉ ይላሉ፡፡የቅርብ ጊዜ የፖለቲካ ሐልዮት ፈላስፋ የሆነው ጆን ራውል ስለ ተረጋጋና በአግባቡ ስለተደራጀ ግዛት አንዲህ በማለት ይናገራል፡፡ “እውነተኛ ሰላም በመሀከላቸው አለ፤ የምንለው  ባለበት በሚረጋው  ትክክለኛ አመክንዮ ሁሉም ማኅበረሰቦች ስለሚረኩ ነው፡፡” የቡሽ ዶግማ (bush doctrine) ተብሎ በሚጠራው የአሜሪካ የውጭ ግንኙነት ፓሊሲም ዴሞክራሲ ሲስፋፋ ሰላም እንደሚመጣ ያትታል፡፡ ፡ አማናዊ ሰላም ናፋቂዎች ግን ለምናባዊ ፍትሕ እና ለተረጋጋ ግዛት (ideal justice and stable state) ግንባታ ሲባል ጦርነት መካሔዱን ይነቅፋሉ፡፡
           አራተኛው አስተሳሰብ ደግሞ ሰላም የጦርነት ተቃራኒ ብቻ አይደለም በማለት ይሟገታሉ፡፡ የተለያዩ እምነቶች ራስን በመንፈስ ከፍ ከማደረግ ጋርም ያያይዙታል፡፡ሰላም የጦርነት አለመኖር ብቻ አይደለም የሚሉት ዳላይ ላማ  “ሰላም እርስ በርስ ከመግባባት ሌሎችን ከመታገስ እና መብታቸውን ማክበር ላይ በተመሰረተ  የደህንነት ስሜት እና የህሊና በአርምሞ መርጋት ነው” ይላሉ፡፡ክርስቲያኖች ደግሞ የቅዱስ ጳውሎስ  ወደ ፊልጵስዩስ ሰዎች በሰደደው መልዕክቱ ላይ ያሰፈረውን “አእምሮንም ሁሉ የሚያልፍ የእግዚአብሔር ሰላም ልባችሁንና አሳባችሁን በክርስቶስ ኢየሱስ ይጠብቃል”ን በመጥቀስ ከቡዲህዝም ጋር የተሰናሰለ አመክንዮን ያቀርባሉ፡፡ይሁንና ሰላም ፥ ለአማናዊ ሰላም ናፋቂዎች  እጅን አጣጥፎ በመቀመጥ ብቻ አይመጣም፡፡
      በስኬታማነታቸው እና በህዝቦቹ እና መሪዎቻቸው ቁርጠኝነት እንዲሁም ነውጥ አልባ ትግልን  በመከተላቸው ሁለት ትግሎች ነጥረው ወጥተዋል፡፡ በጋንዲ የተመራው የህንድ የነጻነት ትግል እና በማርቲን ሉተር ኪንግ የተመራው የጥቁር አሜሪካውያን ትግል ፤ለአማናዊ ሰላም ናፋቂዎች አንጀት አርስ ለኛ ለምንዱባን ደግሞ የተስፋ ነጸብራቅ፡፡ ያለ ነውጥ የተጠቁት መጠበቅ ሰላምን ማስፈን እንደሚቻል ለሚያምኑ ሰዎች የእምነታቸው ማጠንጠኛ፡፡
    
   


                                                                                                                             ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስና በሀገራችን እነኚህ ሳይንሳዊ እና ሀይማኖታዊ ወይይቶች(ስለ ዛሬ ነው የማወራው) ጆሮ ተነፍገዋል፡፡ አሁንም አልሰለጠንም፡፡ አንዱ እዚህ ሆኖ “በደደቢት በኩል ኑ” ይላል ሌላው ደግሞ ዳር ቆሞ “በማንኛውም መንገድ (by any means)” ይላል፡፡ይህ ርቀት ያልገባቸው ብላቴናዎች መሀል ቆመው እንግባባ ቢሉ ለእስር ፣ ለእንግልትና ለስደት ተዳረጉ፡፡ ቢቸግራቸው ከሩቅ ሆነው ቅኔ ተቀኙ ፡፡እንዲህ እያሉ
  
አረ ሰው አለቀ፣ ሰው አለቀ በሏት
እሷ (እንኳን) ለታመመ ለሞተም ግድ የላት፤
ትቻት ረስቻት ሆኜ እንደነገሬ
በምን አስታውሻት ሲያመኝ ዋለ ዛሬ…
    
      ብዙዎቻችን ግን የዝምታ ዘመቻ (Silence conspiracy) የሚያመጣውን ቀዉስ አልተረዳንም፡፡ ሰለ ሰላም ለማሰብ ፈላስፋ መሆን አይጠይቅም፡፡ በዕለት ተዕለት ኑራችን የሚያጋጥመን ነው፡፡ እኛ ግን አይናችንን ጨፍነናል፡፡ ሳር ቅጠሉ ግን ሰላም በሀገር እንደጠፋ ያሰረዳሉ፡፡በቤታችን፣ በትምህርት ቤት፣ በመስሪያ ቤታችን፣ በየቤተ እምነቱ የሰላም እና የሰላም  ፍሬ ያለህ በማለት ያሰተጋባሉ፡፡ “ እሰመ ገዝፈ ልቡ ሕዝብ ወዕዘኒሆሙ ደንቀወ እምሰሚዕ፤ ወከደኑ አዕይንቲሆሙ ከመ ኢይርአዩ በአዕይንቲሆሙ፤ ወበዕዘኒሆሙ ኢይስምዑ ወበልቦሙ ኢይለብዉ ወኢይትመየጡ ኀቤየ ወኢይሣሃሎሙ፡፡” ተብሎ ነቢዩ ኢሳያስ የተነገረው ትንቢት በእኛ ተፈፀመ፡፡
    አሁን የምንመካበት የስሙኒ እንጀራን ነገ ላለማጣታችን ምን ዋስትና አለ? ያለእረፍት ሌት ተቀን የምንወልዳቸው ልጆችንስ የት ልናሳድጋቸው ነው? ስንት ወንድም እህቶቻችን ከሀገር ተሰደዱ? በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በተዳላደለ መሰረት ላይ የተገነባ ሰላም ስለሌ የሚባክነውን የትውልድ አእምሮ አስበነዋል? እውነት በህግ ፣ በስርዓት ነግዶ ማትረፍ ይቻላልን? የሀይማኖታችን ትዕዛዛት አፍርሰን ለስንቱ ጉቦ ሰጠን? የምንመካባቸው ገዳማት አድባራት ነገ ለመኖራቸው ምን ዋስትና አለ? (አሁን አሉ አንዴ!?) ዛሬ ታቦተ ፅዮን አንደምትሸጥ እየሰማን ነው እምነ ጽዮን ይብል ሰብዕ ከወዴት ተረሳ? ዛሬ የመንፈሳዊ ምግባራትን ለመፈጸም ተለከለን ነገስ  ?
     ገብቷቸውም ሆነ ሳይገባቸው ከትግራይ አንስቶ(አረ ከኤርትራም ጭምር) ብዙ እናቶች ልጆቻቸውን ገብረዋል፡፡ለቀይ ሽብር ፣ ለነጭ ሽብር ፣ ለህወሓት ፣ ለሻዕቢያ በታጋይነት ፣ ለእናት ሀገር በወታደርነት፡፡   በከንቱ የፈሰሰ ደም ሁሉ የሰማዕት ደም ነው እርሱ ደም ለማፍሰስ ቢንቀሳቀስም እንኳን፡፡ ዳግም ደም እንዲፈስ አንፋልግም ፤ የአንድም ሰው  ፤  የሰላም ትርጉሙ ግን ሊገባን ይገባል፡፡ ሰላም የጥቂት ሰዎች ጉዳይ ብቻ ሳይሆን ሁላችንም የምንታገልለትና እኩል የምንቋደስው መሆን አለበት፡፡ በእብራይስጥ ሻሎም  የሚለው ቃል ሰፊ  ትርጉም አለው፡፡ peace, justice and well being of mankind ሰላም ፍትህ እና የሰው ልጆች በመልካም ሁኔታ መኖር ፤ በመጀመሪያ የሰላም ትርጉሙ ይግባን ከዚያ ማንም እንዲሰጠን አንጠየቅም እድሜ ልካችንን እንታገልለታለን እንጂ!!!
No One Is Free Until we Are All Free it works for Peace also.
አማናዊ ሰላም ለኢትዮጵያ ፣ ለአለማችን ይገባታል፡፡

የኛ ትውልድ-ሁለት

Standard

      ጠንከር ያለ ነገር በተፈራበት በዚህ ወቅት የመጀመሪያውን ክፍል በትዕግስት አንብባችሁ አስተያየታችሁን ለሰጣችሁኝ በሙሉ እግዚአብሔር ወጋችሁን ይክፈላችኹ፡፡የምፈልገውንም አግኝቻለው ችግራችንን ሁሉንም ሆኜ ለመረዳት ሞክሬያለው፡፡ አንድ ያሰደተኝን ነገር ግን አልደብቃችሁም፡፡

አብዛኛውን አስተያየት ከአስተያየት ሰጪው ነጥዬ ባደረኩት መጠነኛ ምልከታ ተስፋ ያደረኩት ነገር ህልም ፣ ቅዠት አለመሆኑን ተረድቻለው፡፡ እውነቴን ነው የምላችሁ የኛ ትውልድ ይለያል ፤ በአስተሳሰብ ከያ ትውልድ ተነጥለናል፡፡እውነት እውነት እላችኃለው ፥ ትንሽ ቅንነት እና አቤላዊነት ብናዋጣ ከሀገራችን ያለፈ ጥቀም በቀቢጸ ተስፋ ለምትኳትነው አለማችን እናበረክታለን ፡፡ አንዲት ትንሽ ነገር ላስረዳ፡፡ የተወሰኑ የትውልዳችንን አንጓዎች ለመግለጽ የተጠቀምኩባቸው እንደ ነጠላ ፣ ኒቃብ ፣ ሂጃብ ፣ መልበስ ጢም ማሳደግ ፣ ጸሎተ ማዕድ ማድረስ የመሳሰሉትን በበጎም ሆነ በክፉ አላነሳሁም ይህን ልዩነት ግልጥ የሚያደርጉ በአፍኣ የሚገለጹ ምግባራት በመሆናቸው ብቻ እንደተጠቀምኩባቸው ተረዱልኝ፡፡

          በክፍል አንድ ወጨጌ ፣ አረብ አስተኔ ፣ ምዕራብ አስተኔ ብዬ የሰየምኳቸውን የትውልዳችን ክፍሎች አይተናል፡፡ በዚህ ጹሑፍ የቀሪውን ዘመን አመጣሽ አንጓ እናያለን፡፡ በመጨረሻም ለውይይት መነሻ የሚሆኑ ፣ የግል አስተያየቶችን በመስጠት አበቃለው፡፡ የተሻለ የመፍትሔ ሀሳብ አለኝ የሚል ካለም ለመቀበል ዝግጁ ነኝ፡፡ሀሳቡ ከኔ የራቀ በመሆኑ ብቻ አልቃወመዉም ፤ ብልግና ፣ ዕብሪት እና ኃላቀርነት (ጌጃ ይለዋል የኛ ትውልድ) ካለው ግን ዘመናችን ነገሮች እጅግ የቀለሉበት ስለሆነ  የራሱን የስድብ ምህዳር እንዲፈጥር በትህትና እንጠይቃለን ፡፡ ራስን በቴክኖሎጂ የማቆር ችግርም ካለ ቴክኒካዊ ድጋፍ እንሰጣለን እድሜ ለመጎልጉል ጎግል፡፡
          በመጀመሪያው  ጽሑፍ ምዕራብ አስተኔ የሚለው ጅምላ ፍረጃ ተስተወሎበታል የሚለውን አስተያየት ያለ ምንም ማንገራገር ተቀብዬዋለው፡፡ መጣጠፉ ከጥናት ፅሑፍ በተለየ ገላጭ ወይም ምስል ከሳች በሆነ መልኩ የተፃፈ ነው፡፡ በመሆኑም በመተንተን ማቅረብ ማሰረዳት አይጠበቅበትም፡፡ አቅሙ እና ፍላጎቱ ያለው ግን ሰፋ አድርጎ ቢያሳየን አልጠላም፡፡ በገጠሪቷ ኢትዮጵያ ያለውን ወጣት ይህ አገላለጽ ይጨምራል ወይ የሚለው አጠያያቂ ነው፡፡ እንደኔ እንደኔ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ካስተዋልኳቸው የገጠሪቷ ኢትዮጵያ ልጆች እንደተረዳሁት ከሆነ ብዙም ከሌላው የትውልዳችን ክፍል ተነጥሎ የወጣ አስተሳሰብ የራቁ አይደሉም ፡፡ አረብ ፣ምዕራብ አስተኔ ወይም ወጨጌ ይሆናሉ ወይም በዘውግ ተሸፍነው ከሚጠዛጠዙት ውስጥ ይመደባሉ፡፡ አለዚያ በሐገራችን ካለው የዳቦ ችግር አኳያ ቀጥሎ የማነሳው ሰፋ ያለውን ቡድን ይቀላቀላሉ፡፡
ዳቦ ይቅደም (Dabo First)

        “ያለምንም ደም ኢትዮጵያ ትቅደም” እየተባለ መፈክር ብቻ የሆነ መፈክር በሚፈከርባት ኢትዮጵያ የተወለደ  ያደገ  አይመስልም፡፡ይህንን ሰው ነጠላ ለብሶ ሲያስቀድስ ፣ ጁምዓ ሶላት ሲሰግድ ፣ ኳየር ሲመራ ልታገኙት ትችላላችሁ፡፡ስለእገሌ ብሔረሰብ ጭቆና ሲያወራ ስለህዳሴው ድልድይ ይቅርታ ግድብ፣ ስለ አላማጣ ኮረም መንገድ ስፋት እና ጥራት ትንታኔ ሲያቀርብ ልታገኙት ትችላላችሁ፡፡የአይጋ ፎረም መጣጥፎች በድርሳነ መለስ ታጅበው ከኪሱ አይጠፉም፡፡ነገር ግን አብዮታዊ ዴሞክራሲ ቀርቶ የኢቲቪ ረጃጅም ድራማዎችና ጥናታዊ መሰል ፊልሞችን መረዳት ለእርሱ ራስ ዳሽንን እንደመዉጣት የከበዱ ናቸው፡፡ የእርሱ ሀሳብ ቀሊልነቱ ሳይታወቅበት  ተሹሞ ቶሎ ቶሎ ራሱን እንዲያለማ ፤ ነገ ለሚክፍተው ሱቅ፣ ከውጭ ለሚያስገባው እቃ ታክስ እንዳይጠየቅ ፣ የትምህርት እና የስራ እድሎችን አሟጦ ለመጠቀም  ብቻ ነው፡፡ከገዢው ፓርቲ በተጨማሪ በተቃዋሚዎችም ዙርያ ሲያንዣብብ ይታያል፡፡  ሚዲያው ከፍተኛ ወረራ ከደረሰባቸው ዘርፎች የሚመደብ ነው (የኢቲቪ አኬልዳማ  ህያው ዳቦ ጋጋሪን ለመመልከት  የሚያስችል የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው)  ቲያትር ፣ ሙዚቃ ፣ ፊልም ኢንዱስትሪው ዳቦ ከመጋገር ውጭ የመንፈስ ልዕልና በማይተይባቸው ምርቶች እና አምራቾች የተመላ ነው፡፡  ይህ ዘውግ መኖሩ የሀሳብ ርትዕነት ላይ ያለው መግባባት ሚዛናዊ እንዳይሆን አድርጎታል፡፡ እውነትን የሙጥኝ ብሎ የተቀመጠው ኪሱም ሞራሉም እንዲጎዳ ሆኗል፡፡ ብላቴናዎችም ምን ላይ መድከም እንዳለባቸው የተሳሳተ ግንዛቤን እንዲይዙ አድርጓቸዋል፡፡ ማኀበረሰቡም የኛን ዘመን ፉርሽካ ነው እንዲል አስገድዶታል፡፡ እውን ፉርሽካ ነን!? ዘመናችንስ!?
በምን እንግባባ?!
           በብዙ ጉዳዮች ላይ ያለን የአቋም መለያየት እንኳን በአንድ የአህጉር ክፍል ቀርቶ በአንድ ፕላኔት ያለን አይመስልም፡፡ ትውልድ ሁሌ በሐሳሳ ውስጥ እንዳለፈ ነው ቦታ እና ጊዜ ሳያግደው ሁሌም ልብን የሚመላ ነገር ይፈልጋል፡፡ራሴን ለራሴ ለማስረዳት ሌሎች አቻዎቼን ለመረዳት ልቤን ባስጨነኩኝ ቁጥር  በአለማችን የተደረጉ ሐሰሳዎች እንድጎበኝ ያሰገድደኛል፡፡ ከሁሉም ግን በሰሜን አሜሪካ እና በካሪቢያን ሀገሮች የሚኖሩ ህዝቦች ያደረጉት ፍለጋ እጅግ ልቤን ይነካኛል ፡፡ብዙዎቻችን የካሬቢያን ሰዎች አጼ ኃይለ ሥላሴን በተለያየ መልክ ከመለኮት ጋር ማዛመዳቸውን ለመረዳት ይከብደናል፡፡ታሪካቸውን ስናጠና ግን ሐሳሳቸው እዚህ እንዳደረሳቸው እንረዳለን፡፡ የነጮቹ ቅጥ ያጣ ብልግና እውነትን እንዲፈልጉ አስገድዷቸዋል፡፡ “ወደ አፍሪካም ተመለከቱ  ጥቁር ንጉስ ዘውድ በደፋ ጊዜ የአርነት ቀን ሩቅ አትሆንም” የምትለው ‘የነብያቸው’ የማርክስ ጋርቬይ ትንቢት እዚህ አደርሷቸዋል፡፡ ቦብ ማርሌም የእርሱም ፣ የኛም ፣ የወገኖቹም ስለሆነችው አለማችን በዘፈኖቹ ፍለጋውን ለማንጸባረቅ ሞክሯል፡፡
Emancipate yourselves from mental slavery
None but ourselves can free our minds
Have no fear for atomic energy
’cause none of them can stop the time
How long shall they kill our prophets?
While we stand aside and look
Some say it’s just a part of it
We’ve got to fulfill the book
     የራዲዮ ጋዜጠኛው Brent Clough የቦብ ማርሌን ድርሻ  እንዲህ ሲል ይገልጸዋል፡፡“For so many people all over the world Bob’s lyrics and music began a process of self discovery, of self awareness. But equally important he offered clues and advice for each person to build a future, different from the one they expected to inherit.”
                                                     
              እኛ ደግሞ በብዙ ጉዳዮች ብንለያይም እንዳቂሚቲ የተወሰኑ ብልጭታዎች ማርከውናል፡፡ የእነዚህ ጊዜያዊ ክስተት ፈጣሪዎችም የዚህ ትውልድ አባላት መሆናቸው ደግሞ ተስፋችንን የበለጠ ያለመልመዋል፡፡ በቴዲ አፍሮ ጃ ያሰተሰርያል “መለየት አቃተን የሚበጀንን ሰው” ብለናል ፤ በይሰማዐከ ወርቁ ዴርቶጋዳ ሀገራዊ እውቀት ፣ እሴት ፣ ልዕልና ፍለጋ ደብረ ብርሃን ሥላሴ ሄደናል ፤ ከበዕውቀቱ ስዩም ጋር “ስልጣን expire date ይኑረውም” ብለናል ፤ ከመሀመድ ሰልማን ጋር ፒያሳ ቁጭ ብለን ማኪያቶአችንን እያጣጣምን ኢቲቪን አውግዘን (በንስሐ እስኪፈወስ ድረስ) ከዐይናችን ለይተናል፡፡በአቤ ቶክቻው ሽሙጦች ሳቅን ከቁዘማችን ጋር ቀላቅለናል፡፡ በያ ትውልድ  አቋም የሚያዝባቸው  አንድና አንድ ነው ፣  የኛ መስመር ፣ ብቸኛ አማራጭ ፣  በመቃብራችን ላይ ፣   በደደቢት በኩል ኑ ፤አሲምባ ላይ አንገናኝ ፤ አብዮታዊት ኢትዮጵያ ወይንም ሞት ምናምን  የሚባልላቸው ነገሮች የምር እና አስፈላጊ እንዳልሆኑም ገብቶናል፡፡ከዚህ ይልቅ ሀሳቦች ሲታረቁ አይተናል፡፡ ከሁሉም ግን አዲስ ነገር ጋዜጣ ከቀልድ እና ቧልት በዘለለ በሰከነ መንፈስ ለሀገር ለወገን ማሰብን አስተምራናለች፡፡የሀሳብ ልዩነት ሊከሰት የሚችል ነገር ግን ቀድመው በበሰሉ ሳይንሳዊ መንገዶች ሊታረቅ እንደሚችል ከልባችን እንድናምን ሞግታናለች፡፡ ደረሰ ጌታቸው “Addis Neger”:Addis Tiwuld  በሚል ርዕስ በፃፈው መጣጥፍ  ይህን መገነዛዘብ እና መረዳዳት (በሀሳብ መግባባት) እንዲህ ሲል ገልጾታል ፡፡ Addis Neger represented the birth pangs of an attempt to go beyond the shackles of polarized political viewpoints at logger heads with each other. It represented a broad church of ideas where such competing ideologies could speak to each other and learn to appreciate each other’s viewpoints.
            
            
       እነዚህን ትንንሽ ጅምሮች አጠናክረን መቀጠል አለብን፡፡ ከሆድ የዘለለ ፣ ትውልድን የሚያርቅ ፣ የሚያግባባ ስራ ለሚሰሩ የትውልዳችን አባላት እና ሌሎች ታላላቆቻችን ተገቢውን ዋጋ እና ክብር መስጠት አለብን፡፡ ጥበብ ፣ ሙያ ፣ ሙያተኛ ፣ የሀይማኖት ተቋማት ፣ የሀይማኖት አባቶች ፣ መምህራን ፣ ልሂቃን ወሊቃውንት ሊያግባቡን ይገባል፡፡ የኛ ትውልድ እርሱ በያዛቸው በራሱ ሜዳ ሲሆን የምር በመድከም ሀላፊነቱን መወጣት አለበት፡፡ የሀይማኖት አባቶች ፣ የጥበብ ሰዎች ትውልድ ተግባብቶ ፍሬያማ እንዲሆን ያላቸውን ተፈጥሯዊ ጉልህ ድርሻቸውን ካልተወጡ እነርሱን በመለመን የእነርሱን ጉስቁልና በመሰለቅ ጊዜያችንን ማባከን አይገባንም፡፡ በመሆን ፣ በማከል ፣ በመብለጥ ክፍተቱን መሙላት አለብን፡፡
ጨዋነት ይፋፋምብን!!!
        ጨዋነት ከሁለት ምንጭ ይቀዳል፡፡ የመጀመሪያው የእምነታችንን መሰረታዊ የስነ ምግባር መርሆች ጠንቅቆ ከመረዳት በእርሱም ከመኖር ሲሆን ፥ ሁለተኛው ከነጻ አስተሳሰብ ፣ የሰው ልጅን በጥቅሉ ማኀበረሰቡን ከማክበር ፣ በህግ እና በስርዓት ለመኖር ከልብ ከመፈለግ ይመነጫል፡፡ የአለማችንን ታሪክ ስንመረመር ጨዋነት በሁለቱ መሰረቶች ውህድ አስተሳሰብ የተገነባ ነው ፡፡ በየዘመናቱ አንዱ አንዱን እየበለጠና እየጋረደ እዚህ ደርሰናል፡፡ በተለይ በምእራቡ አለም የታላላቅ ፈላስፎች መነሳት በዘመነ አብርሆት ዉስጥ ማለፍ ከጥንት ግሪክ ፈላስፎች በመነሳት የተደረጉ ሐሰሳዎች እጅግ ልብን የሚመላ ሀሳቦች እንዲያገኙ ሆኗል፡፡የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን መዳከም እና ከውስጧ ተቃዋሚዎች (Protestantism) መነሳታቸው ጨዋነት እንደገና እንዲተረጎም አድርጎታል፡፡
        በምዕራባዉያን ዘንድ ቢደበዝዝም በሀገራችን ኢትዮጵያ ሀይማኖቶች አሁንም ጠንካራ መግባቢያ ናቸው፡፡ ተሰሚ የበላይነትም አላቸው፡፡ የሞራል ህጎቻችን ምንጭ ፣ አብሮ የመኖራችን ምሶሶ የሴኩላር ማኦኢስት እምነት ካህናት አንደሚነግሩን ፥ እንጨት እንጨት የሚለው ሕገ መንግስት አይደለም፡፡ በዘመናት በዳበረ ፣ የሰው ልጅ በአምላክ በልዩ ሁኔታ መፈጠርን ፤ ምድርን ይጠብቃት ይንከባከባት ዘንድ ፍሬዋን  እየለቀመ ይበላ ዘንድ ወደ አለማችን መምጣቱን ፤ አንድ አምላክ አለምን እንደፈጠረ በመግቦቱ በጠብቆቱ እንደማይለያት ፤ በሚያምኑ ታላላቅ እምነቶች በሚመነጭ የስነ ምግባር ህግ እና ሀይማኖታዊ ትዕዛዛት ነው፡፡ እንኳን secular maoeist አይደለም secular humanist የሆነው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት አለማችንን ማግባባት ፣ ማሰተባበር አልቻልም፡፡ (ዘልዬ ወደ አለም አቀፍ ምሳሌ የመጣሁት የኛ ፣ የትውልዳችን ፣ የሀገራችን ጉዳይ  በሀገር ውሰጥ ባሉ ውጥንቅጦች ብቻ ስለማይወሰን ነው፡፡)
  
        በአለማችን 2.1 ቢሊዮን ገደማ ክርስቲያኖች ፣ 1.5 ቢሊዮን  ሙስሊሞች ፣ 900 ሚሊዮን ሂንዱዎች ፣ 367 ሚሊዮን  ቡዲስቶች ፣  በርካታ ኮንፊሽንስቶች ፣ ሺንቶዎች ፣ ይሑዲዎች እንዲሁም ሌሎች እምነቶች  ይገኛሉ፡፡  ከዚህ አሀዝ የምንረዳው ከሰማንያ በመቶ በላይ የአለም ህዝብ ሀልዎተ ፈጣሪን የሚቀበል ነው፡፡ በሀይማኖት ለሚኖር ህዝብ አረማዊ መፍትሔ መፈለግ ደግሞ ሁለት ሞግዚት ያለው ህጻን በእሳት ይቃጠላል የሚለውን የሀገሬ ሰው ብሂልን ያስታውሰኛል፡፡ ለዚህም ይመስላል ከሌላኛይቱ ሞግዚት መታገል እንደማይገባቸው ያመኑት የበርማው ተወላጅ  ዩ ታንት ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት በተጨማሪ የተባበሩት ሃይማኖቶች ምክክር መድረክ አንደሚያሰፈልግ በፅንኦት የተናገሩት፡፡ ትንቢት ብንለውስ !? (ምንም እንኳን ለአስር አመታት በዋና ጸሐፊነት ያገለገሉት ድርጅት ባይቀበላቸውም)
        

      የጨዋነት አስፈላጊነትን ማንሳት ያስፈለገው ምድራችን በክፉ እና ባለጌ ሰዎች ስለተመላች ነው፡፡ ጤናማውን የተፈጥሮ ሚዛን ለመጠበቅ ደጋግ ሰዎች አምላካቸውን (አምላከ ሙሴ ፣ አምላክ ጳዉሎስ ፣ አምላከ መሐመድ ፣ አምላከ ዞራስተር ፣ አምላከ ሶቅራጠስ) እየተማጸኑ ብዙ መስራት ፣ መድከም ይጠበቅባቸዋል፡፡ የአለማችንን ሀብት ምድሪቱ የምታበቅለውን ዘር ፍሬ ተካፍለን እንደመብላት ጉልቤ ህያው ሆኖ ይኖራል (the fittest will survive) እያለን እስከ መቼ እንተላለቃለን፡፡

        ከኛ ትውልድ ብዙ ይጠበቃል፡፡ በአጉል አርበኝነት መንፈስ ያላዋቂ ሳሚ እንዳንሆን ጥንቃቄ እና ጨዋነት ያስፈልጋል፡፡የእምነታችንን ዶግማ በደንብ እንመርምር፡፡ ግራህን ለመታህ ቀኝህን ስጥ የሚለውን አምላካዊ ትዕዛዝ አንዳልሰማ ሆነን ሙስሊም ወንድም እህቶቻችንን በድለናልን ?  እውን የኛ አባቶች በክርስቲያን መሪዎች ስለተጨቆኑ ነው እንዲህ ሰላማዊ በፍቅር ነዋሪ የሆኑት? ወይስ እስላም ፣ ሰላማ ፣ ሻሎም ፣  ሰላም የሚለውን ቃል በተግባር ኖረውበት ? እውን ይህች ሀገር ከትምህርተ ሃይማኖቱ እና ትውፊቱ (religious doctrine and tradition) በዘለለ አውሮጳዊ ስነ ምግባር የሞራል ህግ ያስፈልጋታልን? እውን ከቁስ በቀር ፕሮቴስታንታዊ ይትበሃል አውሮጳን እና አሜሪካን ጠቅሟል ? እውን አንዱ ዘውግ(የብሔር ፣ የሃይማኖት ፣ የፓለቲካ) አንዱን ሲጨቁን ኖራልን? በታሪክ አጋጣሚ እኛ ተጨቆነ የምንለው ከሌሎች ነጥቀን የራሳችን የምናደርገው ወገናችን ጨቋኝ አልነበረምን? እነዚህ ሁሉ የኛን የበሰለ መልስ የሚፈልጉ ጥያቄዎች ናቸው፡፡

 ታሪክን ፍልስፍናን ሳይንስን በደንብ እንማር አንመርምር፡፡ እድል ቢሰጠን መምራት ቀርቶ ገንቢ ሐሳብ መለገስ እንችላለንን? ይህ የተፈጠሮ ግዴታ ነው ከጥቂት አመታት በኃላ ያ ሀገሪቱን አንደ የውስጥ ደዌ ነቀርሳ ያቆሰላት ትውልድ በእድሜ ፣ በጤና መድከሙ አይቀርም፡፡ ታዲያ በአርአያው እና በአምሳሉ የቀረጻቸው አዳዲስ ጅቦች ሀገሪቱን ይረከቡ መፍቀድ የለብንም፡፡ በጭራሽ!!! ታዲያ ጫፍ አና ጫፍ(polarization)  ልዩነትን ፣ ብልግናን እና ምን አገባኝን ትተን ለሰው ልጆች ነጻነት ፍትሕ አና ሰላም ቁርጥ አቋም ይኑረን፡፡
          ባንድ የአዲስ ነገር ጋዜጣ ጽሁፉ አብይ ተ/ማሪያም ሰመሀል መለስ ዜናዊ አስረስን በአንድ ጉባዔ እንዳያት ገልጾልን ነበር፡፡ ያኔ ምነው እነዚህ ውድ የኢትዮጵያ ልጆች ተቀራርበው ስለእናታቸው ኢትየጵያ መፃኢ ተስፋ በመከሩ ብዬ አሰብኩኝ ፡፡ሳሚ አርከበ እቁባይን እና ተከስተ ስብኃት ነጋ አብረው የተነሱትን ፎቶ  ተመለከትኩኝ ፡፡ አውን ከእነዚህ የኢትዮጵያ ልጆች ፣ የትውልድ አቻዎቼ ጋር ተወያይተን የማንፈታው ችግር ይኖራልን ስል ህሊናዬን ጠየቅኹት ያገኘሁት መልስ ግን በምንም ተዓምር የሚል ነበር፡፡ ምክንያቱም እኔ ከአባቴ ጋር ያለኝ ግንኙነት ጠንቅቄ አውቃለው ይሄ ጥሩ ያኛው ደግሞ መጥፎ እያለ ከፉና ደጉን እንድለይ አድርጓል ፡፡ ታዲያ አሁን ከፈጣሪ ለጥቆ በድሀ አቅሙ ሁሉን አሟልቶ ላሳደገኝ አባቴ ክብር ይግባውና በጥቂት ጉዳዮች ላይ ከእርሱ የተሻለ ግንዛቤ ይኖረኛል፡፡ ዘመኑ የኛም አይደል! ታዲያ  በቤተዘመድ በጨዋታ መሐል ባንዳንድ ጉዳዮች ላይ ባለው አመለካከት እንደእኔ የሚበሽቅ ማንም የለም፡፡ ሌላ ትንታኔ መስጠት ትችላላችሁ እኔ ግን የተረዳሁት አንደዚህ ነው፡፡ በልጅነት የትክክል ነገር ሚዛን በእኔ ህሊና አባቴ ነበር፡፡ ያ ማንነቴ ጎልብቶ ነው እዚህ የደረስኩት፡፡ስለዚህ የአባቴን ስህተት ለመለየት ከማንም የተሻለ መመዘኛ አለኝ፡፡ ያ ትውልድን ሩቁ አድርጎ የሚያስብ ካለ አጅግ ተሳስቷል፡፡ የኔም ያንተም አባት  እናት አጎት ነው፡፡ ለስህተቱም ለበጎ ምግባሩም ሀላፊነቱን ይወስዳሉ፡፡   በጎውን ነገር ተቀብለን ፣ ክፉን መጣል ፣ አይነታውን መቁራት ፣ የተበደለን መካስ ፣ የተሰደደን ሀገር ሰላም ነው እውቀትህን ነዋይህን ባገር አፍስስ ብሎ መጥራት ፣ የደከመን በወጉ ማሳረፍ (ወዲ ዜናዊንም ጭምር) ፣  አረጋውያንን ደግሞ መጦር ይጠቅብናል፡፡
ብርሃናችሁ በሰው ፊት ይብራ (keep reflecting)
            ብዙ ማሰብ የሚችሉ ብዕር ለመጨበጥም አቅም የማያንሳቸው ወዳጆች አሉኝ፡፡ እኔንም ከ ‘“መ” ህጎች’ መታቀብን እንድመርጥ የፍቅር ምክራቸውን በመለገስ ምክንያታችን በዋናነት እነኚህ ናቸው በማለት ይናገራሉ፡፡ የመጀመሪያው አሁን በለጋ አእምሮ በጫጫርነው ነገር ነገ አለአግባብ እንጠቀሳለን (misquoted) ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ አሁን ያለን ያልረጋ (fluid) አስተሳሰብ የተሳሳተ ቢሆንስ በማለት ሀሳባቸውን ያቀርባሉ፡፡ ማለፊያ ነው፡፡  ለኔ ግን ዝምታዬ ነው የሚቆጨኝ ፡፡ ሞኝ አድርጎ የፈጠረኝ አምላክ ይመስገን፡፡ አልተመቸኝም ብዬ በመንፈራገጤ ያጣሁት ነገር የለም ፤ አለማወቄን እንድረዳ ፣ ጉድለቴን እንድሞላ ፣ የሚደርገኝ ይሄ መፍጨርጨር ነው፡፡ይህ እድሜያችን የምድር አበቦች የሆኑ ህጻናትን የምንከባከብበት ታላላቆቻችንን የምናደምጥበት (ያውም የምር ታላቅ ከተገኘ) እኛ ግን አንደ አጠቢያ ኮከብ የምናበራበት ነው፡፡ ለኔ በዚህ ዘመን ከዋጋ ግሽበቱ ፣ ከኑሮ ውድነት በላይ የሀገር ሰዎች እጥረት ያሳስበኛል፡፡ ለዕውቂያ ቀለብነት (for the benefit of being celebrity ) ካልሆነ በቀር ማን በጎ ነገር ይስራል ሊቃናቱስ ከወዴት አሉ ? ባይሆን ካሉበት ተበሳጭተው ልጅ ያቦካው ብለው  እንዲመጡ እናደርግ እንጂ!!! 
  
                አንዳንድ ከሶ አደሮች በክፉ ተመለከቱት እንጂ ዜሮ ነጥብ አምስት በመቶ የኢንተርኔት ዘለቄታ(penetration) ባላት ሀገራችን በሳይበር የሚደረግ ተዋስኦ (discourse) ኢትዮጵያን ይወክላል ለማለት አያስደፍርም  ፡፡ ከዚህ ወስጥ ምን ይህሉ የኮረዶችን ፎቶ በማየት ጊዜያቸውን እንደሚያጠፉ ማርክ ዙከርበርግ ይቁጠራቸው፡፡ትንሽ ለውይይት መነሻ የሆኑ ሀሳቦችን ለመገበያየት ምሁራዊ የውይይት ባህልን ለማዳበር ትረዳናለች፡፡ ከማሰብ እና በቀን ውስጥ የተወሰኑ ሰዓታትን መስዋዕት ከማድረግ በቀር ሌላ ነገር አለመጠየቋ በጎ ፈቃደኞችን (volunteerism) እንዲተጉ ታደርጋለች፡፡ Volunteers are the only human beings on the face of the earth who reflect this nation’s compassion, unselfish caring, patience, and just plain love for one another ያለው ማን ነበር ?
              አቶ መለስ ዋናው ጠላታችን ድህነት ነው ይላሉ፡፡ እኔ ግን እነዚህ ናቸው ባይ ነኝ፡፡ little knowledge, ignorance negeleigence እውነትን አንጻፍ ፤ እዉነትን እንኑር ፤ሐይማኖት መጽሐፍትን የምር እንመርመር ፣ ለአለም አቀፍ እና ሀገር አቀፍ ኪራይ ሰብሳቢዎች ራሳችንን አሳልፈን እንስጥ፡፡ታሪክን እናጥና ከእርሱ ለመማር ስህተትን ላለመድገም ቢያንስ ቢያንስ ንቁ ተሳተፊ መሆን ይገባናል (active tiwtter facebooker googler blogger) በመጨረሻ ታላቁ  ፈላስፋ ሶቅራጠስ ለአቴናውያን በተናገረው ላብቃ The hour of departure has arrived, and we go our ways—I to die, and you to live. Which is better God only knows.

ኢትዮጵያዊ ሰዶማዊ አይደለምን?

Standard
ይድረስ ለኮሜዲያን የሐይማኖት መሪዎች እና ጦማሪያን
ግብረ ቀንድ አውጣ
   ወጣ ከዛጎሉ፤
ገባ ከዛጎሉ፤
            ሁሉም ቀንዳውጣ ነው፤ ዛጎል ነው ባካሉ፤
        ብቅ ጥልቅ ይላል፣ የቀንዳውጣ አመሉ፤
        ፍርሃቱና ጉራው፣ አብረው ይጠልቃሉ፤
      ደስታና መከራው፣ እኩል ይዘልቃሉ፡፡
ወጣ ከዛጎሉ፤
               
                          ገባ ከዛጎሉ፤
                                                  የቀንዳውጣ ኑሮ የቀንድ አውጣ አመሉ፤
                                                ፀጥ ሲል መመዥረጥ  ኮሽ ሲል ከሽሉ፡፡

 ይስማዕከ ወርቁ፣ የቀንድ አውጣ ኑሮ፣ 2002 ዓ.ም.፣ 
አዲስ አበባ
           
          የግብረ ሰዶማዊያን ልምድ ለማካፈል ወደሀገራችን መምጣትን ተከትለው የተዘገቡ ሁለት አይነት  ዜናዎች አሉ፡፡የመጀመሪያው የሀይማኖት አባቶች መርሐ ግብሩን ለመቃወም የጠሩት ስብሰባ ለሌላ ጊዜ መራዘሙን የሚገልጽ ሲሆን (ዝም ብላችሁ ተቀመጡ የምትል ቀጭን ትዕዛዝ እንደደረሳቸው በውሰጠ ታዋቂነት ይመዝገብ)  ሁለተኛው ደግሞ የተለያዩ ጦማሪያን በመረጃ መረብ እና ሌሎች መገናኛ ብዙኃንን ተጠቅመው ቅድስት ሀገራቸውን እንዳትጎድፍ ከሰዶማዉያን ስብከት እንድትጠበቅ  ያሰሙት ድምጽ ናቸው፡፡ የልባችንን፣ የልባቸውን የነገሩንን እነ ማህሌት ዘሰለሞንን አይጨምርም፡፡
          ታላቁ የሙሴ መጽሐፍ ኦሪት ዘልደት የሰዶም ሰዎችን እንዲህ ሲል ይገልጻቸዋል፡፡ “የሰዶም ሰዎች ግን ክፉዎችና በእግዚአብሔር ፊት እጅግ ኃጢአተኞች ነበሩ።”  ከዚህ የምንረዳው የሰዶም ሰዎች ችግር በተመሳሳይ ጾታ መካከል የሚደረግ ግንኙት ብቻ ሳይሆን እጅግ ብዙ የሆኑ በእግዚአብሔር ፊት ኃጢአተኞች እና ክፉ ያሰኟቸው እኩይ ምግባራት እንደነበራቸው ነው ፡፡

         ይህን ዘርፈ ብዙ  ችግር የተሸከመች ሀገራችን ኢትዮጵያን ያዩ  ICASA  ሰዎች  ዳቦ ቆርሰው ሰዶም ብለው ሰየሟት፡፡ እናም በዚህም አላበቁ ስለ ተመሳሳይ ጾታ ግንኙት ያላቸውን ልምድ ሊያካፍሉን መጡ፤ ቺርስ እንደማለት፡፡ እነዚህ ሰዎች እውነት አላቸው ድሀ የሚበደልባት፣ ፍርድ የሚጓደልባት፣ ትንሽ እውቀት አቆር ጋዜጠኛ ሲነሳ ካገር እንዲሰደድ መላ የሚፈልግባት፣ ወደ ሰማይ ከፍ ከፍ እንዳለችው እንደ  ቅፍርናሆም ፣ ወዮልሽ  እንደተባሉት ኮራዚ እና  ቤተ ሳይዳ ብትሆንባቸው ነው፡፡ አብርሐም ሰዶም ስትቃጠል አገሪቱ  እንደ እቶን ስትነድ ፣ ጢስ ሲነሣ እንዳየው የሚነደው የማን ዘር ነው? ኢትዮጵያዊ ሰዶማዊ አይደለምን? ከኬንያ እስከ ደቡብ አፍሪካ፣ በሶማሊያ(ሱማሌም የሚሰደዱባት ሀገር ሆና)፣ በጅቡቲ፣ በሱዳን፣ በሁሉም የሰሜን አፍሪካ አገሮች፣ በሁሉም የመካከለኛው ምስራቅ ሀገሮች ከፍተኛ የሰብዓዊ መብት ጥሰት የሚፈጸምባቸው፤  በአውሮጳ ፣ በሰሜን አሜሪካ የሚኳትነው ኢትዮጵያዊ አይደለምን? በሽርሙጥና ገላቸውን የሚቸረችሩት የኛ እህቶች አይደሉምን? ሜድትራኒያን፣ ቀይ ባህር ፣ ህንድ ውቅያኖስ ደሙን የሚገብረውስ ማን ሆኖ ነው? ታዲያ ግብረ ሰዶማውያን ወደ እኛ ቢመጡ ያስገርማልን?
         እኔ  መርሐ ግብሩን የተመለከተ ምንም አይነት አስተያየት የለኝም፡፡ ከእርሱ ይልቅ እጅግ ያበገነኝ የመጤ ሰዶማውያን ጉዳይ ሳይሆን የሀገር በቀል ሰዶማውያን ጉዳይ ነው ፡፡ ሰው ከሰውነት በታች ሲኖር፣ የኑሮ ሚዛኑ ተዛብቶ ማኀበራዊ ቀውስ ሲነግስ የት ጠፍታችሁ ከርማችሁ ነው ? አሁን አዛኝ ቅቤ አንጓች የምትሆኑት ? የድሀ አደጎችን ሆነ የመበለቲቷን ድምጽ መች አደመጣችሁት? ኖላዊነቱ  ቀርቶ በታሪካዊ አጋጣሚ እንድታስዳድሩት  የሆናችሁትን ተቋማት መች በቅጡ ጠበቃችሁ? ትንንሽ ሰዶምን አልገነባችኹምን? እናንተ ጸሐፊያን፣ ማኀበራዊ ሐያሲ ነን ባዮችስ የቀንዳውጣ ስልትን የምትከተሉ አሁን በማሪያም ከዛጎላችሁ መውጫ ጊዜ ነውን? ይህንን የሰዶማዊያን ጉባኤ ቀርቶ ሰዶማዊያንን ለመተቸት የሚበቃ የሞራል የበላይነት አላችሁ? ሌላው ቢቀር በቅርቡ የተደረጉትን  ትንሽ ፣ ትልቁ ፣ የምር ለማሰብ ሙከራ ያደረገውን፣ ብዕሩን አንግቦ ወደ እንግሊዝ የዘመተን ተማሪ ሳይቀር በሽብርተኝነት ሲፈረጁ አንዲት ቃል  ከአንደበታችሁ ወጣች?  ብዕራችኹስ አንዲት አረፍተ ነገር ጫጫረች? ህዝብን ለማሸበር የሀገር ሰዎችን ለመክሰስ ከ አስራ ሶሰት አመት በታች የማይመለከተው ሆረር ፊልም ሲሰራ በዝምታችሁ ይሁንታን አላጎናጸፋችሁትምን ?ይህንን አይን ያወጣ አፈና ባለመቃወማችሁ የሰዶም ሐጢአት ተባባሪ ያደርጋችኋል፡፡ ሰዶም ላይ ተቀምጠን ሐጢአቷን እና መቀማጠሏልን እንዳላየ አልፈን ከሌላ ቦታ ሰዶማዊ መጣ፤ መግለጫ ሰጠ፤ ልምድ አካፈለ ብንል አያምርብንም፡፡ ማሰተባበያ እንደትሰጡን አንፈልግም እንደለመዳችሁት ይህ የመቅለል እና የመቃለል ዘመን አስኪያልፍ ዛጎላችኹ ውስጥ ጠብቁን ፡፡ከቻላችሁ የምላስ እና ብዕር ወለምታውን ሰብስቡት ሌላ የኔ ቢጤ ደሀ ጨጓራ፣ አንጀት፣ ጉበት እንደይታመም አታሰራጩት፡፡ እባካችሁ ያልበላንን አትከኩልን፡፡መዠመሪያ መቀመጫዬን አለች ዝንጀሮ፡፡ በአንድ ወቅት በንጹሕ ኢትዮጵያውያን ደም የቀለደ ቦለቲከኛ እንግሊዝ ቢደርስ በዚያ የሚገኙ አትዮጵያዉያን እንዲህ እያሉ ተቀብለውታል shame on you!!!!!!!!!!!!! Shame on you በዚሁ አበቃው shame on you!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!!
ቀንዳውጣ በሙሉ፣ ምነው ምን ሆነሃል?
የፍርሃት ብዛት፣ ዛጎል ሰርቶብሃል፤
ልውጣ አልውጣ እያልህ፣ ያሽቆጠቁጥሃል፤
ምን ያንበጫብጭህ፣ ያሰደነብርሃል?
መቃብርህን እደሁ፣ ተሸክመኸዋል፡፡